አቶ ኢሳያስ ከበደ በሆራይዘን ፕላንቴሽንስ ስር በነበረው በኢትዮ አግሪ ሴፍት ስራ አስኪያጅነት በኋላም በአዲስ አወቃቀር በተደራጀው ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ውስጥ በግብርና ዘርፍ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚነት ጡረታ እስከወጡበት ድረስ በጠቅላላው ለ10 ዓመታት አገልግለዋል።
አቶ ኢሳያስ በአገልግሎት ዘመናቸው በዘርፉ ስር ያሉት ድርጅቶች ሁለንተናዊ እድገት እንዲያስመዘግቡ የላቀ አመራር ሰጥተዋል።
በሸራተን አዲስ ሌግዠሪ ሆቴል በተካሔደው የሽኝት ፕሮግራም ላይ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አህመድ ባደረጉት ንግግር አቶ ኢሳያስ ለስራ ተፈጥረው በስራ የኖሩ፤
በአመራር ዘመናቸው የተረከቧቸውን ድርጅቶች ውጤማና አትራፊ ያደረጉ፤

እጅግ ታማኝና ትጉህ መሪ በመሆናቸው ከእርሳቸው መለየት ከባድ መሆኑን በማንሳት ወደፊትም ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ቤታቸው መሆኑን ገልጸዋል።
አቶ ኢሳያስ ከበደም በበኩላቸው በተደረገላቸው የአሸኛኘት ፕሮግራም መደሰታቸውን በመግለፅ መላ የግሩፑን አመራሮችና ሰራተኞች አመስግነዋል፡፡
ከሀገር ወዳዱና ባለራዕዩ የድርጅቱ ባለቤትና ሊቀመንበር ሼይኽ መሐመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲን ፍጹም የስራ ነጻነት አግኝተው በመስራታቸው ክብር እንደሚሰማቸውም አቶ ኢሳያስ ተናግረዋል፡፡
ከተቋሙ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አህመድም ያገኙት የሥራ ላይ እገዛና ልምድም ላስመዘገቧቸው ውጤቶች ከፍተኛ ሚና እንደነበረው በመግለጽ ሚድሮክን በአጠቃላይ ዩኒቨርሰቲ ነው ሲሉ ገልጸውታል፡፡
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በሚፈልጋቸው ጊዜና ሁኔታ ሁሉ ከጎኑ እንደሆኑ አረጋግጠዋል፡፡
አቶ ኢሳያስ ከበደ ለተተኪያቸው ለአቶ ፈለቀ ታደሰ የስራ ርክክብ ያደረጉ ሲሆን አቶ ፈለቀ ታደሰም ከርክክቡ በኋላ ባደረጉት ንግግር ከአቶ ኢሳያስ ጋር ባሳለፏቸው ጊዜያት በብዙ መልኩ ከእርሳቸው ከፍተኛ ልምድ እና እውቀት ማግኘታቸውን በመግለጽ የለውጥ አሻራቸውን ለማስቀጠል ቃል ገብተዋል።
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕም ላደረጉት የላቀ አመራር ክብር በመስጠትና ለቀሪው የጡረታ ዘመናቸው መልካም ምኞት ለመግለጽ በዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ ጀማል አህመድ አማካኝነት በኤሌትሪክ የሚሰራ ዘመናዊ ቮልስ ዋገን አይ ዲ 6 (ID.6) መኪና በስጦታ አበርክቶላቸዋል።

የስራ ባልደረቦቻቸውም አቶ ኢሳያስ በግብርናው ዘርፍ ያካበቱትን ሰፊ የስራ ልምድ እና እውቀት ለሐገራቸው እንዲያበረክቱ በመጠየቅ ቀሪ ዘመናቸውን በሙሉ በጤንነት እንዲያሳልፉ መልካም ምኞታቸውን ገልፀዋል።
በፕሮግራሙ ላይ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አህመድን ጨምሮ የየዘርፎቹ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚዎች፣ የግብርና ዘርፍ የስራ ባልደረቦቻቸውና የተወከሉ የዋናው መ/ቤት ሰራተኞች እንዲሁም ቤተሰቦቻቸው ተገኝተዋል።
በመርሀ-ግብሩ ላይ አቶ ኢሳያስ ከበደ ለሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ያበረከቱትን አስተዋጽኦ የሚያስቃኝ አጭር ዶክመንተሪ ፊልም ለታዳሚያን ቀርቧል፡፡
በመጨረሻም የኬክ ቆረሳ፣ የማስታወሻ ፎቶግራፍ አነሳስና የእራት ግብዣ ተከናውኗል።