ሐገራችን ኢትዮጵያ በቀንድ ከብት ብዛት ከአፍሪካ ቀዳሚ እንደሆነች ይታወቃል። የወተት ምርት ሊሰጡ የሚችሉ በርካታ የዳልጋ ከብቶችንም ይዛ ትገኛለች። ይሁን እንጂ ከዚህ ሀብት ከፍተኛ ተጠቃሚ ሳትሆን ለረጅም ጊዜያት ቆይታለች።
ከዚህም በመነሳት በወተት እና የወተት ውጤቶች ላይ ያሉ ችግሮችና መፍትሄዎች ላይ ያተኮረና ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ጋር በመተባበር የተዘጋጀ የፓናል ውይይት በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ ኔክሰስ ሆቴል ተካሂዷል።



በዉይይቱ ላይ ዶ/ር አሻግሬ ዘዉዱ በአ.አ. ዩኒቨርስቲ የምግብና ስነ ምግብ ማዕከል ተባባሪ ፕሮፌሰር፣ ዶ/ር ዘላለም ይልማ ከኤስኤንቪ ብሪጅ ፕሮጀክት ማናጀር፣ አቶ ታሪኩ ተካ በእ/ል/ኢ/ የእንስሳት ምርትና መኖ ማቀናበር እና ጥራት ምርምር ዘርፍ አስተባባሪ፣ አቶ ፋሲል ኃይለኛው በላሜ ዴይሪ የግዢና አቅርቦት ስራ አስኪያጅ በፓናሊስትነት ተሳትፈዋል።
በመድረኩ ላይ ወተት እና የወተት ውጤቶች ለጤናማ እድገት ያላቸው አስተዋጽዖ የተነሱ ሲሆን ለምርታማነት መቀነስ መንስኤ የሆኑ ጉዳዮቸ በስፋት ተዳሰዋል።
እነዚህም ተግዳሮቶች:-
- በማምረቻ ማዕከላት ያሉ ቴክኒካዊ ችግሮች
- ጥራቱን የጠበቀ የመኖ አቅርቦት አለመኖር
- የእንስሳት ጤና አገልግሎት አለመዘመን
- አስተዳደራዊ ችግሮች (የመሠረተ ልማት፣ የብድርና የፓሊሲ)
- የወተት ከብቶች ዝርያ
- የእንስሳት አያያዝና እንክብካቤ ችግር እንደምሳሌነት የተነሱ ሲሆን መፍትሔ ሊሆኑ ይችላሉ የተባሉ ሃሳቦችም ተጠቁመዋል።
እነርሱም:-
- ወተት በክላስተር ማምረት
- የወተት አምራች መንደሮችን መገንባት
- የተሻሻሉ ዝርያዎችን ማስፋፋት
- የእንስሳት ጤና አጠባበቅና አያያዝን ማስፋት
- የወተት መሰብሰቢያ ማዕከላትን ማዘመን
- ለአነስተኛ ወተት አምራቾች ተከታታይ ስልጠናዎችን መስጠት
- የወተትን ጥራትና ብዛት ሊያሳድጉ የሚችሉ የፖሊሲ መዕቀፎችን ማዘጋጀት የሚሉት ተጠቁመዋል
በሐገራችን 40 የወተት ማቀነባበሪያ ማዕከላት ያሉ ሲሆን ከነዚህ ማዕከላት አንዱ የሆነውንና በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ስር የሚገኘውን ላሜ ዴይሪን የያዘው ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ይህን የፓናል ውይይት በማዘጋጀቱ ከፓናሊስቶችና ከውይይቱ ተሳታፊዎች ምስጋና ተችሮታል።