የሶስትዮሽ ስምምነቱን ከአዲስ አበባ ከተማ ጤና ቢሮ እና ከኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት አገልግሎት ጋር ዛሬ ተፈራርሟል።
ማሽኖቹ ለ180 የኩላሊት ታካሚዎች አገለግሎት የሚሰጡ ሲሆን ድጋፉ ለዳግማዊ ምኒልክ ኮምፕሬንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል የሚደረግ ነው ።
ሚድሮክ እንቨስትመንት ግሩፕ ግንቦት 28/2016 ዓ.ም አዲስ አበባ
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከአዲስ አበባ ጤና ቢሮ እና ከኢትዮጵያ መድሐኒት አቅራቢ አገልግሎት ጋር ለኩላሊት ሕመምተኞች የሚያገለግሉ 10 የዲያልስስ ማሽኖችን ከሶስት አመት የሪኤጀንት አገለግሎት ጋር ለመግዛት ነው ስምምነት የተፈራረመው።
ስምምነቱን በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ የማህበራዊ ኃላፊነትና የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አምባሳደር አሊ ሱለይማን፣ የአዲስ አበባ ከተማ ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶከተር ዮሐንስ ጫ እንዲሁም በኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት አገልግሎት የግዥ አስተዳደር ምክትል ስራ አስፈፃሚ አቶ ሰለሞን ንጉሴ ተፈራርመዋል።

ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በሀገር ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጋር መሰል ሰው ተኮር ስራዎችን በጋራ እየሰራ በመሆኑ ድርጅቱ ደስተኛ መሆኑን አምባሳደር አሊ ሱለይማን ተናግረዋል።
እንዲህ አይነት ማህበረሰቡን የሚጠቅሙ ተግባራት የሊቀ-መንበራችን ሼይኽ መሐመድ ራዕይ በመሆናቸው ዋና ስራ አስፈፃሚያችን አቶ ጀማል አህመድ በትኩረት የሚከታተሉትና በዳይሬክቶሬት የሚመራ መሆኑን አስረድተዋል።
ስምምነቱ በኩላሊት ህመም እየተሰቃዩ የሚገኙ ዜጎችን ህይወት ለመታደግ እንደመሆኑ አቅም ያለው ሁሉ በሚችለው መንገድ መረባረብ እንዳለበትም ዳይሬክተሩ አሳስበዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶከተር ዮሐንስ ጫላ በበኩላቸው ሚድሮክ ሁሌም ለሀገር ግንባር ቀደም ደራሽ ከመሆኑ ባሻገር ከተማ መስተዳድሩ በሚሰራቸው የልማት ስራዎች ሁሉ በመሳተፍ የማህበረሰቡን ኑሮ ለማሻሻል እያደረገ ላለ ጥረት ምስጋና አቅርበዋል።
ማሽኖቹ በአጭር ጊዜ ተገዝተው ለታካሚዎች እንዲደርሱ በከፍተኛ የኃላፊነት ስሜት እንደሚሰሩ የገለፁት ደግሞ በኢትዮጵያ መድኃኒት አቅርቦት የግዥ አስተዳደር ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ሰለሞን ንጉሴ ናቸው።
ሚድሮክ ከወራት በፊት በተመሳሳይ በ40 ሚለዮን ብር ወጪ 10 የዲያልስስ ማሽኖችን ከስድስት ወራት የ”ሪኤጀንት” ግብዓት ጋር መለገሱ ይታወሳል።








