ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ነሐሴ 23 ቀን 2015 ዓ.ም አዲስ አበባ
የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከፍተኛ አመራሮች ባደረጉት ውይይት በስድስቱም ዘርፎች የተመዘገበው ውጤት አበረታች መሆኑን ነው የገለጹት፡፡
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በ2015 በጀት ዓመት የሥራ አፈጻጸም ከባለፈው የተሻለ እንደነበርም ተጠቁሟል፡፡
በዓመቱ የተገኘው ሽያጭም ካለፈው አመት ጋር ሲነፃፀር በ43% በመቶ እድገት ማሳየቱ በውይይቱ ላይ ተጠቅሷል፡፡
ድርጅቱ በበጀት ዓመቱ የዕቅዱን 94.5 በመቶ ማሳካቱም ተገልጿል፡፡
ውይይቱን የመሩት የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አህመድ በጀት አመቱ አዳዲስ ፋብሪካዎች ተመርቀው ሥራ የጀመሩበትና ትልቅ ኢንቨሰትመንት የሚጠይቁ ግዙፍ ፕሮጀክቶች ግንባታም የተጀመረበት እንደነበር ተናግረዋል፡፡
በተለይም በአዲስ አበባ ከተማ የሚገነባው መሐመዲያ ቪሌጅን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች በመገንባት ላይ ያሉ ሆቴሎች ግንባታ ተጨማሪ የሰው ኃይል የሚፈልጉ በመሆኑ ድርጅቱ በሃገሪቱ ያለውን የስራ አጥ ቁጥር በመቀነስ ረገድ አይነተኛ ሚናውን እየተወጣ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በአሁኑ ሰዓት ለ67,921 ዜጎች የሥራ እድል የፈጠረ መሆኑን ነው ዋና ሥራ አስፈጻሚው የተናገሩት፡፡
በተጨማሪም የድርጅቶችን ምርታማነት ከማሻሻል አንጻር፡-
ድርጅቶችን በዕቅድ ላይ ተመስርቶ ዉጤታማ በሆነ መልኩ ለመምራት፣
በእህት ድርጅቶች መካከል የገበያ ትስስር ለመዘርጋት፣


ወጪ ከመቀነስ እና ሌሎች የድርጅቶቹን ምርትና ምርታማነት ለማሻሻል የሚረዱ ተግባራት በአመቱ በተሻለ መልኩ መከናወናቸው በመድረኩ ላይ ተገልጿል፡፡
ተቋሙ ከኢኮኖሚያዊ አስተዋጽኦዉና እንቅስቃሴዉ ባሻገር የተለያዩ ማህበራዊ ግዴታዎችን ለመወጣት የሚያስችሉ አስተዋጽኦዎችንም አበርክቷል፡፡
በዚህም መሰረት በበጀት ዓመቱ ከ1.2 ቢሊየን ብር በላይ በገንዘብና በአይነት የሚገለጹ የማህበራዊ ድጋፍ ስራዎችን አከናዉኗል፡፡
በውይይቱ ላይ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ 6 ዘርፎችን የሚመሩ ምክትል ዋና ሥራ አስፈጻሚዎችና የኮርፖሬት ዳይሬክተሮች የሚመሩትን ዘርፍና ክፍል የእቅድ አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበው ውይይት ተደርጎበታል፡፡
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በማኑፋክቸሪንግ፣ በግብርና፣ በመዓድን፣ በንግድና አገልግሎት፣ በሆቴልና ሪዞርት እንዲሁም በኮንስትራክሽንና ሪል ስቴት ሥር የተደራጁ 44 ኩባንያዎችን ያቀፈ ተቋም ነው፡፡
በውይይቱ ላይም የተገኙ ውጤቶች፣ ያጋጠሙ ችግሮችና የመፍትሔ አቅጣጫዎች ላይ ሰፊ ምክክር ተደርጎባቸዋል፡፡