“በጎነት የመኖሪያ መንደር”ን መርቀዉ የከፈቱት የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ክብርት ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አህመድ እና አቶ ሰዒድ አሊ የልደታ ክፍለ ከተማ ስራ አስፈፃሚ ናቸው።


በምርቃት ስነ-ስርዓቱ ላይ የከተማ አስተዳደሩ እና የክፍለ ከተማው የስራ አስፈፃሚ አባላት፣ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከፍተኛ አመራሮች፣ መኖሪያ ቤቶቹ የተገነባላቸው አካላት እና ጥሪ የተደረገላቸ እንግዶች ተገኝተዋል።
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ጋር በመተባበር በልደታ ክፍለከተማ የገነባቸው እነዚህ ሁለት ባለ G+8 የመኖሪያ ህንፃዎች 140 የመኖሪያ ቤቶችን የያዙ ሲሆኑ ከ18 ዓመታት በላይ በቆርቆሮ ቤት ውስጥ ሲኖሩ የነበሩና በልማት ምክንያት ተነሺ ለሆኑ የከተማዋ ነዋሪዎች የተዘጋጁ ናቸው።
ከንቲባ አዳነች አቤቤ “ከነበራችሁበት ችግር እና ሰቆቃ ወጥታችሁ ለዚህ ስለበቃችሁ እንኳን ደስ አላችሁ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ለጠየቅነው ጥያቄ መሠረት ፈጣን ምላሽ በመስጠት ገንብቶ አስረክቦናል፡፡
አቶ ጀማል አህመድ ይሄ ስራ በምድር የሚያስመሰግን ብቻ ሳይሆን በሰማይም የሚያፀድቅ ነው በማለት በስራቸው ከሚገኙ ሰራተኞቻቸው ጋር ቀን ከሌት በመስራት በአጭር ጊዜ ውስጥ አጠናቆ ለተጠቃሚዎች በማስተላለፉ ላመሰግን እወዳለሁ” ብለዋል።
አቶ ጀማል አህመድ ባደረጉት ንግግር “በቆርቆሮ ቤት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎችን የሚያስቃኝ ዶክሜንታሪ ፊልም ካየን በኋላ ይህን ህይወት መቀየር አለብን በሚል እነዚህን ህንፃዎች ሰርተን በማስረከባችን ፍፁም ደስተኞች ነን።

ሊቀመንበራችን ሼይህ መሀመድ እንዲህ ያለ ማህበረሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎች ተሰርተው ሲመለከቱ ደስ ይሰኛሉ በመሃከላችን ሆነውም አብረውን የሚደሰቱበት ቀን እንደሚመጣ ተስፋ አደርጋለሁ፥ ሁላችሁም ፀሎት አድርጉላቸው” ብለዋል።
መኖሪያ ቤቶቹ ለተጠቃሚዎቹ በዕጣ ተላልፈዋል።
በዛሬው ዕለት ተጠናቀዉ ከተመረቁት ሕንፃዎች በተጨማሪም ግንባታቸው እየተከናወነ የሚገኙ ሁለት ባለ 10 ወለል ሕንፃዎች ያሉ ሲሆን ግንባታቸው ሲጠናቀቅ 180 አባወራዎችን ተጠቃሚ ያደርጋሉ።
በዚህም በዛሬው ዕለት ተመርቀው ለአገልግሎት ከበቁት መኖሪያ ቤቶች ጋር በድምሩ የ320 አባወራዎችን የመኖሪያ ቤት ችግር ይፈታሉ።
የመኖሪያ መንደሩ በውስጡ ተደራጅተው ነዋሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ 48 የእንጀራ መጋገሪያ ምጣዶች፣ የሴቶች እና የወንዶች የፀጉር ሳሎኖች፣ 12 የልብስ ስፌት መኪኖች እንዲሁም የህፃናት ማቆያ የተሟላለት ነው።





ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ማህበራዊ ኃላፊነቱን ለመወጣት ሕብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ አያሌ ፕሮጀክቶችን ይደግፋል።
በአዲስ አበባ ከተማ 3 በጅግጅጋ 1 የምገባ ማዕከላትን በመክፈት ዓመቱን ሙሉ የኢኮኖሚ አቅም ውስንነት ላለባቸው የሕብረተሰብ ክፍሎች በቀን አንድ ጊዜ የምገባ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል።
ለሌሎች ታላላቅ ሃገራዊ ፕሮጀክቶችም ከፍተኛ ድጋፍ የሚያደርግ ሲሆን ለለሚ የእንጀራ መጋገሪያ ፋብሪካ 75 ሚሊዮን ብር እንዲሁም በቅርቡም ለ”#ጽዱኢትዮጵያ” 64 ሚሊዮን ብር ድጋፍ ማድረጉ ይታወሳል።










