ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ በስድስቱም ዘርፎቹ በ2017 በጀት ዓመት በስራቸው የላቀ አፈጻጸም ላስመዘገቡ ሰራተኞችና አመራሮች የዕውቅናና የሽልማት ፕሮግራም አካሂዷል፡፡
ተቋሙ የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ 588 ሰራተኞቹ ለእያንዳንዳቸው ከ100 እስከ 500 ሺህ ብር ስጦታም አበርክቷል።
ሽልማቱን የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ጀማል አህመድ እና የየዘርፉ ምክትል ዋና ስራ አስፈፃሚዎች ለተሸላሚዎች ሰጥተዋል።


በፕሮግራም ላይ የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ባለቤትና ሊቀ-መንበር ሼይኽ መሀመድ በቀጥታ በዙም ሚቲንግ ለተሳታፊዎች ባስተላለፉት መልዕክት ምኞቴ የዋጋ ንረትን በመከላከል ድሃው እንዳይሰቃይ ማድረግ ነው ብለዋል።
የኔ ጀግና እና የምኮራበት የሚድሮክ የልማት ሰራዊት እንኳን ደስ አላችሁ በማለት የህዳሴው ግድብ መጠናቀቅ ለእኛም ለልማታችን ስለምንፈልገው የኢትዮጵያ ህዝብ ኩራትና ክብር ነው። እንኳን ደስ አለን! እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
ሚድሮክ ባለፉት አምስት አመታት ያስመዘገበው ውጤት በጣም የሚያኮራ ነው በማለት የተቋሙ ሰራተኞች እና አመራሮች ላከናወኑት ተግባር ምስጋና አቅርበዋል።
በተለይም ሚድሮክ አሁን ላይ 79 ሺህ ሰራተኞች ያለዉ መሆኑን ገለፀው ቁጥሩን በእጥፍ ለማሳደግ መሰራት እንዳለበት አሳስበዋል።
የኢትዮጵያ ሰራተኞች ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ሀገር ነው በማለት ሰው ተኮር ስራዎችን በመሰራት የሚታወቅ ተቋም መሆኑንም ገልፀዋል ።



የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ጀማል አህመድ ሚድሮክ ባለፉት አምስት አመታት ምርትና ምርታማነትን በመጨመር በሀገሪቷ ኢኮኖሚ ውስጥ የአንበሳውን ድርሻ ይዞ መቀጠል ይጠበቅበታል ብልዋል።
ሚድሮክ የመንግስት ደሞዝ ማሻሻያን ተከትሎ የድርጅቱን ዝቅተኛ መነሻ ደሞዝ 6,100 ብር ማድረጉን ገልፀው በ2017 በጀት አመት ከ1.1 ቢሊየን ብር በላይ ለማኅበራዊ ኃላፊነት ወጪ ማደረጉን ገልፀዋል።
ዋና ሥራ አስፈጻሚዉ አቶ ጀማል አህመድ በዛሬው እለት ከሁሉም ድርጅቶች ተሸላሚ የሆኑ አመራርና ሰራተኞች ለተቋሙ ስኬታማ ጉዞ ምክንያት በመሆናቸው አመስግነዋል።
በሚሊኒየም አዳራሽ በተካሄደው በዚህ የእውቅና እና የሽልማት መርሃ ግብር ላይ ከ6,500 በላይ ሰራተኞች ተሳትፈዋል።










