በሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ እና በዳሽን ባንክ ወጪ የተገነባውና “ተስፋ ብርሃን አሙዲ የምገባ ማዕከል” የተሰኘ በቀን አንድ ጊዜ እንኳን መመገብ የማይችሉ የአዲስ አበባ ነዋሪዎችን የሚመግብ ማዕከል ተመርቀ፡፡

በአዲስ አበባ ከተማ፣ በአዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ፣ ተክለ ሃይማኖት ተብሎ በሚጠራው አካባቢ የተገነባው ይህ ማዕከል በከተማዋ ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ የክብር እንግዳነት ተመርቋል፡፡ የምርቃት ሥነ-ሥርዓቱ ሀሙስ ግንቦት 5 ቀን 2013 ከተከበረው የኢደል ፊጥር በዓል ጋር በደማቅ ሁኔታ ተከናውኗል፡፡
የምገባ ማእከላቱን መክፈት ያስፈለገው በተለያየ ምክንያት ለማህበራዊ ችግር የተጋለጡ ወገኖችን ለመመገብ በማሰብ መሆኑን ምክትል ከንቲባዋ አስረድተዋል:: ችግሩ የሁሉም ኢትዮጵያዊ በመሆኑ መፍትሄውንም በጋራ ማምጣት በማስፈለጉ በልዩ ሁኔታ የምገባ ማዕከላቱን በ5 የተመረጡ ክፍለ ከተሞች ለመክፈት እየተሰራ መሆኑንም አክለው ገልጸዋል፡፡
ወ/ሮ አዳነች “ዜጎች የእለት ጉርሳቸውን አጥተው ከቆሻሻ ላይ ምግብ እያነሱ ሲመገቡ ማየት የዜግነት ክብርን የሚነካ ነው” ካሉ በኋላ፤ ይህንን ችግር ለመቅረፍ የምገባ ማዕከል ለመስራት የፕሮጀክቱን ሃሳብ ለባለሀብቶች ባጋሩበት ወቅት ፈጥነው ምላሽ ለሰጡት የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ለአቶ ጀማል አህመድና ለግሩፑ ሰራተኞች አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡
ማዕከሉ ለዚህ እንዲበቃ ላሳዩት ቁርጠኝነትና በሃገር ልማት ላበረከቱት አይተኬ ሚና የሚድሮክ ሊቀ-መንበር ሼህ ሙሀመድ ሁሴን አሊ አል-አሙዲ አለማመስገን ንፉግነት እንደሆነ ወ/ሮ አዳነች በዚሁ ወቅት ተናግረዋል፡፡